በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::
በስዊዘርላንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ኦፕፊኮን/ ዙሪክ ውስጥ በ1992 ዓ.ም. (እ.አ.አ.2000) ተመስረተች:: በተለያዩ ምክንያቶች ስዊዘርላንድ በመምጣት ነዋሪ የሆነው የተዋሕዶ እምነት ተከታይ ቁጥር እየጨመረ በመሄዱ እንደ ሌሎች ተቋማት ሁሉ የቤተ ክርስቲያናችን መኖር በእጅጉ አስፈላጊ በመሆኑ የቸሩ እግዚአብሔር ፈቃድ በሆነበት በዚህ ወቅት ሊቋቋም በቅቷል:: ማንም ሊገምት እንደሚችለው ሁሉ ውጣ ውረድ ያልነበረበት ጉዞ አልነበረም ጉዟችን:: በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ በመጀመርያይቱ የሐዋርያው የጳውሎስ መልእክት ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች ምዕራፍ 1 ቁጥር 12 ላይ "ይህንም እላለሁ: እያንዳንዳችሁ እኔ የጳውሎስ ነኝ ፥ እኔስ የአጵሎስ ነኝ ፥ እኔ ግን የኬፋ ነኝ ፥እኔስ የክርስቶስ ነኝ ትላላችሁ:: ክርስቶስ ተከፍሏልን?..." እንዳለው መከፋፈል የሌለባት የተዋሕዶ ልጆች በሙሉ የሚያገለግሏትና የሚገለገሉባት ቤተ ክርስቲያን እንድትሆን ያለን ፍላጎትና የተደረገውም ጥረት ሰምሯል ለማለት ይቻላል:: ዛሬ የደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በየሳምንቱ እሑድ በሯን ለምእመናን ልጆቿ ትከፍታለች:: ታላላቅ በዓላት ይከበራሉ፤በስዊዘርላንድ የዓለም ኦርቶዶክሳውያን ማሕበር መስራች አባል ብቻ ሳትሆን ለሁለተኛ ጊዜ ተመርጣ የሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ አባልም ናት:: በዙሪክ የክርስትና እምነት ተቋማት ድምፅ ሰጪ አባል ናት:: በዚህ ዓመት አስረኛ ዓመት በዓላችንን ሰፋ ባለ ሁኔታ ለማክበር በዝግጅት ላይ እንገኛለን:: በዚህ ድሕረ ገጽ አማካይነት ሂደቶችን ለተወዳጅ አንባቢዎቻችን እየተከታተልን እናቀርባለን::
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ታሪክ በይበልጥ ለመረዳት እዚህ ላይ ይጫኑ
|